በመኮንን አልማው!
በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሶስት ሀገራት አስተናጋጅነት የሚካሔደው የ2026 አለም ዋንጫ ውድድር ከአሁኑ መነጋገሪያ የሆኑ ጉዳዮች በዝተውበታል።
በተለይ ከሶስቱ አዘጋጅ አገራት መካከል ዋነኛዋ የሆነችው አሜሪካ ያሻትን ውሳኔ እያሳለፈች ነው።
በተለይም በፖለቲካው ዓለም በተፋጠጠቻት እና በግልጽ ጦርነት ከገጠመቻት ኢራን ላይ አስከፊ በደሎችን እያደረሰች ነው ተብሏል።
በዓለም ዋንጫው ለሚሳተፈው የኢራን ብሔራዊ ቡድኑ ስብስብ የተሳትፎ ቪዛ ላለመስጠት ስትታሽ የከረመችው እና በመጨረሻም በርካታ ለልዑኩ ቡድን ከልክላ በከፈል ፍቃድ የሰጠችው አሜሪካ ለቡድኑ ተሳታፊነቱን ብታረጋግጥም ነገር ግን በርካታ መብቶቹን ነፍጋለች።
"ታሪካዊ ጠላታችን ኢራን በአለም ዋንጫው ሰበብ አሸባሪዎችን እንድታስገባ አልፈቅድም" የምትለዋ አሜሪካ የኢራን ብሔራዊ ቡድን አባላት ፈፅሞ በአሜሪካ እንዳያድር መከልከሏ ይታወቃል።
ኢራን ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎቿን በአሜሪካ ምድር የምታደርግ ቢሆንም ነገር ግን አሜሪካ አዳር የሚከለክል ቪዛ ነበር የሰጠቻት።
በዚህም ኢራን ጨዋታዋን በዕለቱ ወደ አሜሪካ አምርታ ጨዋታው ሲያልቅ በቀጥታ ከአሜሪካ የምትወጣ ይሆናል።
በ2026ቱ የዓለም ዋንጫ ላይ ለመሳተፍ ሜክሲኮ የገባው የኢራን ልዕክ ቡድን በበኩሉ የአሜሪካ ቪዛ በመዘግየቱ እና አንዳንድ የልዑኩ አባላት ፍፁም በመከልከሉ የተሰማውን ከፍተኛ ቅሬታ ገለጿል።
ቡድኑ በቱርክ የነበረውን ዝግጅት አጠናቆ ያለፈው እሁድ በሜክሲኮ ድንበር ወደምትገኘው ቲጁአና ከተማ የገባ ሲሆን የኢራን እግር ኳስ ፌዴሬሽን የአሜሪካን ውሳኔ "በስፖርት ውስጥ የተደረገ አስከፊ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት" ሲል ኮንኖታል።
ከአሜሪካው ቪዛ መዘግየት ባሻገር የፌዴሬሽኑን ፕሬዚዳንት ጨምሮ 15 የብሔራዊ ቡድን አባላት ቪዛ ተከልክለዋል።
የቡድኑ ዋና አሰልጣኝ አሚር ጓሌኖይ እና አምበሉ ኢህሳን ሀጅሳፊ በሰጡት አስተያዬት የቪዛው መዘግየት በሰዓቱ የሚያደርጉት የልምምድ ዝግጅታቸው ላይ ተጽዕኖ ማሳደሩን ገልጸው፣ ለዚህም ፊፋ አሜሪካን ተጠያቂ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።
ይህ እየሆነ ባለበት ሰዓት ዛሬ በወጣ አዲስ መረጃ አሜሪካ ኢራን ላይ ሌላ ተጨማሪ ክልከላ አውጃለች። ለኢራን ብሔራዊ ቡድን ደጋፊዎች የቀረበው የስታዲየም መግቢያ ትኬት በድንገት መሰረዙ ተዘግቧል።
ትኬቱ በምን ምክንያት እንደተሰረዘ በአሁኑ ሰዓት ይፋዊ ምክንያት አልተነገረም። የኢራን እግርኳስ ፌዴሬሽን ባወጣው መግለጫ ቡድኑ ማግኘት የሚገባውን የትኬት ኮታ መከልከሉን ተቃውሟል።
ውሳኔውን “ በተሳታፊ ሀገራት መካከል ያለውን የውድድር የእኩልነት መርህ የሚቃረን ነው“ ሲል አውግዟል። ፌዴሬሽኑ አክሎም ፊፋ የገለልተኝነት እና ፍትሀዊነት መርሆችን እና የተቋሙን ደንብ ያክብር ሲል ጠይቋል።
በዚህም ምክንያት የኢራን ብሔራዊ ቡድን ደጋፊዎች ቡድናቸውን ለማበረታታት በዓለም ዋንጫው የማይገኙ ይሆናል። ኢራን በበኩሏ እንደሌሎች የአለም ዋንጫ ተሳታፊ ሀገራት ሁሉ የሷም መብት እንዲከበር እየጠየቀች ሲሆን ነገር ግን ከፊፋም ሆነ ከአሜሪካ የተሰጣት ተገቢ ምላሽ የለም።
በቀጣይ የሚፈጠረውን ተከታትለን ወደእናንተ እናደርሳለን።