የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሓኖም በደቡብ አፍሪካ በተቀሰቀሰው የዘረኝነት ጥቃት የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን በመግለጽ ግድያውና የንጹሃን መፈናቀል በአስቸኳይ እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል።
በደቡብ አፍሪካ በዚህ ሳምንት በተቀሰቀሰው የጥቃት ማዕበል ቢያንስ አምስት ኢትዮጵያውያን እና አምስት ሞዛምቢካውያንን ጨምሮ የበርካታ ንጹሃን ሕይወት መጥፋቱን ዶክተር ቴዎድሮስ ገልጸዋል።
በሺዎች የሚቆጠሩ ቤተሰቦች ከቀያቸው መፈናቀላቸውን እና በሺዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ስደተኞችም ለሕይወታቸው በመሰደድ ላይ መሆናቸውን ያስታወሱት ዋና ዳይሬክተሩ ጉዳዩን "ልብን የሚያደማ" ሲሉ ገልጸውታል።
የጥቃቱ አሳሳቢነት እየጨመረ በመምጣቱ መቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በፓርላማ ፊት ለፊት ሰልፍ በመውጣት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል።
ዶክተር ቴዎድሮስ ባስተላለፉት መልዕክት ይህ በደቡብ አፍሪካ እየተስተዋለ ያለው የዘረኝነት ጥቃት አገሪቱ ከያለፈችበት የአፓርታይድ የነጻነት ትግል ታሪክ ጋር የሚቃረን እና የጋራ እሴቶችን የካደ "አሳዛኝ ክህደት" እንደሆነ አስረድተዋል።
በ1962 ዓ.ም ኢትዮጵያ ለነልሰን ማንዴላ የጉዞ ፓስፖርት በመስጠት ሌሎች የአፍሪካ አገራትም በፖለቲካ እና በፋይናንስ ድጋፍ ለአፓርታይድ መፈረስ ላደረጉት አስተዋጽኦ ይህ ድርጊት ተገቢ አለመሆኑን ጠቅሰዋል።
ማንኛውም አለመግባባት ወይም ቅሬታ በሕግ እና በፍትህ ሥርዓት እንጂ በቡድን ጥቃት ወይም በጅምላ ቅጣት መፈታት እንደሌለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።
በደቡብ አፍሪካ እየተባባሰ ያለው የጥቃት ማዕበል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሀገሪቱን የደህንነት ሁኔታ አሳሳቢ ያደረገው ሲሆን ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ በህገ-ወጥ ስደት ላይ ጠንከር ያለ እርምጃ እንደሚወስዱ ቃል ከገቡ በኋላ ባለፈው አንድ ሳምንት ብቻ 2 ሺህ 7መቶ45 የውጭ ሀገር ዜጎች ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል።
የሃገሪቱ መንግስት ወደ ሀገራቸው ከተመለሱት መካከል አብዛኞቹ በህገ-ወጥ መንገድ ይኖሩ የነበሩ መሆናቸውን ገልጿል።
ከ30 በመቶ በላይ በሆነ ከፍተኛ የስራ አጥነት መጠን የምትታወቀው ደቡብ አፍሪካ ከሦስት ሚሊየን በላይ የውጭ ዜጎችን ማለትም ከጠቅላላው የህዝብ ብዛት 5.1 በመቶ የምታስተናግድ አገር ናት።
ይሁን እንጂ በቅርብ ሳምንታት በዱላ፣ ጅራፍ እና ጋሻ የታጠቁ ቡድኖች መኖሪያ ፈቃድ የሌላቸው የውጭ ዜጎች እስከ ሰኔ 30 ድረስ ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ መስጠታቸውን ተከትሎ፣ የናይጄሪያ፣ ማላዊ፣ ጋና፣ ዚምባብዌ እና ሞዛምቢክ ዜጎች በፍቃደኝነት ወደ ሀገራቸው የመመለስ ሂደትን እየተቀላቀሉ ይገኛሉ።
መንግስት በበኩሉ የስደተኛ መጠለያ ካምፖችን የማያስተዳድር እና በጊዜያዊነት የማቋቋም እቅድ እንደሌለው አስታውቋል።
በመጨረሻም ዶክተር ቴዎድሮስ "ደቡብ አፍሪካም ሆነ አፍሪካ የተሻለ ነገር ይገባቸዋል" በማለት የጥላቻ ንግግሮች በአስቸኳይ እንዲቆሙ የተጎጂዎች ደህንነት እንዲጠበቅ እና የጋራ የሰው ልጅ መብቶች እንዲከበሩ ጥሪ አቅርበዋል።