በኢትዮጵያ የፌዴራል መንግሥት በጀት ባለፉት ጥቂት ዓመታት በብር ሲሰላ ከፍተኛ ጭማሪ ማሳየቱ ቢታወቅም በተመሳሳይ ጊዜ በዶላር ሲሰላ የታየው ለውጥ ግን ዝቅተኛ ሆኖ መገኘቱ ተመላክቷል።
ከ2013 ዓ.ም በኋላ በኢትዮጵያ የነበረው የበጀት ዕድገት በብር ሲሰላ እስከ 480 በመቶ የደረሰ ቢሆንም ይህ በጀት በዶላር በመለወጥ ሲሰላ የዕድገቱ መጠን የ8 በመቶ ጭማሪ ብቻ በማሳየት ዝቅተኛ ሆኖ ተገኝቷል።
በሁለቱ መገበያያ ገንዘቦች መካከል ያለው የዕድገት ልዩነት በግልጽ እንደሚንፀባረቀው ከሆነ የፌዴራል በጀት በ2013 ዓ.ም 476 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን በ2019 ዓ.ም ወደ 2.3 ትሪሊዮን ብር ከፍ ብሏል።
ከ2013 ዓ.ም ጀምሮ የተመዘገበውን የበጀት ዕድገት ስንመለከት በ2013 ዓ.ም 476 ቢሊዮን ብር፣ በ2014 ዓ.ም 561 ቢሊዮን ብር፣ በ2015 ዓ.ም 786 ቢሊዮን ብር፣ በ2016 ዓ.ም 801 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም በ2017 ዓ.ም ወደ 971 ቢሊዮን ብር ከፍ ብሏል።
ይህ የበጀት ዕድገት በ2018 ዓ.ም ወደ 1.9 ትሪሊዮን ብር የተጠጋ ሲሆን ለ2019 ዓ.ም ደግሞ ወደ 2.3 ትሪሊዮን ብር ደርሷል።
በሌላ በኩል በዶላር ሲሰላ በ2013 ዓ.ም 13.6 ቢሊዮን ዶላር የነበረው የበጀት መጠን፤ በ2019 ዓ.ም 14.9 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ሁኗል።
የፌዴራል መንግሥት ለ2019 በጀት ዓመት ያዘጋጀው 2.339 ትሪሊዮን ብር ረቂቅ በጀት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከሰሞኑ ቀርቦ የነበረ ሲሆን አዲሱ በጀት ከ2018 የ1.9 ትሪሊዮን ብር በጀት አኳያ ዕድገት ቢያሳይም በዶላር ሲሰላ ግን ተቀራራቢ ሆኖ ተገኝቷል።
የበጀት ረቂቁን ለምክር ቤቱ ያቀረቡት የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ በጀቱ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ግቦች ለማሳካትና የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት ሊፈጥር የሚችለውን የኢኮኖሚ ጫና ለመቋቋም ታሳቢ ተደርጎ መዘጋጀቱን አስረድተዋል።
ለ2019 በጀት ዓመት ከቀረበው ጠቅላላ በጀት ውስጥ 1.236 ትሪሊዮን ብር ለመደበኛ ወጪ፣ 568.2 ቢሊዮን ብር ለካፒታል ወጪ፣ 520.6 ቢሊዮን ብር ለክልሎች የበጀት ድጋፍ እንዲሁም 14 ቢሊዮን ብር ለክልሎች የዘላቂ ልማት ግብ ማስፈጸሚያ የተመደበ መሆኑ ተገልጿል።
በበጀት ዓመቱ የፌዴራል መንግሥት ጠቅላላ ገቢ 1.817 ትሪሊዮን ብር እንዲሆን ግምት የተወሰደ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 1.6 ትሪሊዮን ብር ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች ለመሰብሰብ ታቅዷል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በበኩላቸው የቀረበው ረቂቅ በጀት የመንግሥትን የልማት ዕቅዶች ለማሳካት ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ ለፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር ዕይታ መርተውታል።
ይሁን እንጂ በብር እና በዶላር የተያዘው የበጀት መጠን መካከል ያለው ይህ ሰፊ የዕድገት ክፍተት በኢኮኖሚው ውስጥ እየታየ ያለውን የዋጋ ግሽበትና የብር የመግዛት አቅም መዳከም ነጸብራቅ እንደሆነ እየተገለጸ ነው።