በመካከለኛው ምስራቅ እየተባባሰ የመጣው የጂኦፖለቲካዊ ቀውስ በዓለም አቀፍ የባሕር ትራንስፖርትና ወሳኝ የንግድ መስመሮች ላይ ከፍተኛ የደህንነት ስጋት በደቀነበት በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ንብረት የሆነችው “አሶሳ” መርከብ ተልዕኮዋን በስኬት በማጠናቀቅ አዲስ ታሪክ መሥራቷ ተሰምቷል።
በቀጠናው ባለው ውጥረት ምክንያት ከፍተኛ የደህንነት ስጋት ባለበት የሆርሙዝ ሰርጥ አካባቢ የኢትዮጵያዋ “አሶሳ” መርከብ ሁሉንም ተግዳሮቶች በማለፍ ከሆርሙዝ ሰርጥ በቅርብ ርቀት ላይ ወደምትገኘው ስልታዊዋ የኮርፋካን ወደብ በሰላም መድረስ ችላለች።
መርከቧ ለኢትዮጵያ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እጅግ አስፈላጊ የሆኑ ጭነቶችን የያዘች ሲሆን ከእነዚህም መካከል የሕክምና ቁሳቁሶችና መድኃኒቶች እንዲሁም ልዩ ልዩ የንግድ ጭነቶች ተጠቅሰዋል።
መርከቧ እነዚህን ጭነቶች በስኬት ከጫነች በኋላ በከፍተኛ ጥንቃቄና ሙያዊ ብቃት ወደ ዋና የባሕር በር ወደሆነችው አጎራባች ሀገር ጅቡቲ ወደብ በሰላም መመለስ ችላለች።
ይህ የተመዘገበው ስኬት የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስን አስተማማኝ አገልጋይነትና አጋርነት በተግባር ያሳየ ነው ያለው ተቋሙ የባሕረኞቻችንን ቁርጠኝነት እና የኢትዮጵያን የባሕር ሎጅስቲክስ ብቃት በተግባር ያረጋገጠ ታሪካዊ ክስተት ሆኖ መመዝገቡን አስታውቋል።
ቀደም ብሎ ተቋሙ መርከቧ በዓለም አቀፍ ውቅያኖሶች ላይ በመጓዝ ላይ መሆኗን ገልጾ የነበረ ሲሆን ከሰሜን አውሮፓ ጥልቅ የባሕር ወደቦች ጀምሮ እስከ ዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች ድረስ ያለውን ትስስር እያጠናከረና በመላው ዓለም የሚካሄደውን ዓለም አቀፍ ንግድ እየደገፈ እንደሚገኝ አስፍሯል።
የሆርሙዝ ሰርጥ በፋርስ ባህረ ሰላጤ እና በኦማን ባህረ ሰላጤ መካከል የሚገኝ እጅግ ጠባብ ነገር ግን በዓለም ላይ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ስልታዊ የባሕር መተላለፊያ መስመር እንደሆነ ይታወቃል።
መስመሩ በዓለም ላይ ከሚንቀሳቀሰው አጠቃላይ የነዳጅና የነዳጅ ውጤቶች ጭነት ውስጥ አንድ ሶስተኛው የሚያልፍበት በመሆኑ ለዓለም ኢኮኖሚ እና ለዓለም አቀፍ የንግድ ሰንሰለት የጀርባ አጥንት ተደርጎ ይወሰዳል።
ይሁን እንጂ በአካባቢው ባለው የጦርነት ውጥረት ምክንያት የሆርሙዝ ሰርጥ እና አቅራቢያው የሚገኙት እንደ ኮርፋካን ያሉ የወደብ ቀጠናዎች ላይ መጓዝ ጥብቅ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን የሚጠይቅ ሆኗል።
በተጨማሪም ተቋሙ በዓለም አቀፍ የባሕር ንግድ እና ሎጅስቲክስ ውስጥ ያለውን አቋም ለማጠናከር በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ውስጥ 16 አዳዲስ መርከቦችን ለመግዛት የሚያስችል ታላቅ ዕቅድ ይፋ ማድረጉን አስታውቋል።
በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ያውለበለቡ መርከቦች የሀገሪቱን እያደገ የመጣውን የዲፕሎማሲ ግንኙነት በመጠቀም በዓለም አቀፍ የጉዞ መስመሮች ላይ በብቃት እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ።
ተቋሙ በአሁኑ ወቅት በራሱ ባለቤትነት ስር ያሉ 10 መርከቦችን፣ ወደ 60 የሚጠጉ የተከራዩ መርከቦችን እና ተጨማሪ የቦታ ክፍፍል ስምምነቶችን በማስተዳደር በመላው ዓለም ከ370 በላይ ወደቦች ላይ መድረስ ችሏል።