በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ይፋ ተደርጎ የነበረውና ሁሉንም አሽከርካሪዎች ዳግም ለማሰልጠንና ለመመዘን የታቀደው አወዛጋቢ መርሃ ግብር በዚህ ዓመት እንደማይጀምርና ለጊዜው እንዲቆም መደረጉን የኢትዮጵያ ከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ማህበር አስታወቋል።
የማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን ዘውዱ እንዳረጋገጡት ማህበሩ ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከተው ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ጋር ባደረገው ውይይት መግለጫው ከወጣ በኋላ ባሉት ቀናት ውስጥ ዕቅዱ ትኩረትና ተጨማሪ ውይይት የሚሻ መሆኑ ታምኖበት እንዲዘገይ ተወስኗል ብለዋል።
ቀደም ሲል አዲሱ የብቃት ምዘና በ15 ቀናት ውስጥ እንደሚጀምር ተገልጾ የነበረ ቢሆንም አሁን ላይ ግን አሰራሩ በዚህ ዓመት እንደማይተገበር ማረጋገጫ መገኘቱን አቶ ሰለሞን ዘውዱ ገልጸዋል።
ስራ አስኪያጁ ማህበራቸው ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጋር ስላደረገው ንግግር ሲያስረዱ የሚያሰለጥኑት እነማን ናቸው እንዲሁም እንዴት መካሄድ አለበት የሚል ጥያቄ ማህበሩ ማንሳቱንና በቀጥታ ስለጉዳዩ መወያየቱን ተናግረዋል።
በዚህም ስልጠናው በዚህ አመት ዓመት የሚሰጥ እንዳልሆነ የታወቀ ሲሆን ቀደም ብሎ በ15 ቀን ውስጥ ይጀምራል ተብሎ የነበረ ቢሆንም ጉዳዩ ትኩረት እና ውይይት የሚሻ መሆኑ ስለታመነበት ለጊዜው “ፖዝ” ተደርጓል ብለዋል።
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ማንኛውም አሽከርካሪ በዚህ የብቃት ማረጋገጫ ሂደት ውስጥ ማለፍ ያለበት መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በቅድሚያ ግን ማንኛውም የሕዝብና የጭነት ተሽከርካሪ የሚያሽከረክሩ አሽከርካሪዎች ምዝገባ፣ ሥልጠና እና ምዘና በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር ማስታወቁ ይታወሳል።
ይሁን እንጂ ማህበሩ እንደዚህ አይነት አስገዳጅ መመሪያዎች ከመውጣታቸው በፊት ሰፊ ጥናት መደረግ እንዳለበትና በቀጥታ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በተለይም አሽከርካሪዎች መሳተፍ እንዳለባቸው እንደሚያምን ተናግረዋል።
በተጨማሪም ለ30 እና 40 ዓመታት በአስቸጋሪ የረጅም ርቀት መንገዶች ላይ ያሽከረከሩ ባለሙያዎችን ከመፈተን ይልቅ የአሽከርካሪዎች ትክክለኛ ፍላጎት ምን እንደሆነ መጠናት ይኖርበታል ያሉ ሲሆን ፈተናው ቴክኒካዊ ወይስ ስነ ምግባር ላይ ያተኮረ መሆን አለበት የሚለው በግልጽ መለየት እንዳለበትም ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል ምዘናው ኤስዲኤስ ድራይቪንግ ስኪልስ በተባለ አንድ የግል ተቋም ብቻ እንዲሰጥ መወሰኑና በ15 ቀን ውስጥ ተፈትነህ የብቃት ማረጋገጫ ካላገኘህ ትባረራለህ የሚሉ ድንገተኛ መረጃዎች መሰራጨታቸው ተገቢ እንዳልነበረ ማህበሩ መግለጹን ከሸገር ሬዲዮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
መንግስት አስገዳጅ ሁኔታዎችን ብቻ ከማውጣት ይልቅ ቁጥጥር የሚደረግበትን ወጥ አሰራር መዘርጋት እንዳለበት ያሳሰበው ማህበሩ በአሁኑ ወቅት አሽከርካሪዎች ቀድመው እንዲዘጋጁ ለመርዳት የራሱን የስልጠና ሞጁሎች የማዘጋጀት ስራ እያከናወነ እንደሚገኝ አስታውቋል።
መንግስት ራሱ የሰጠውን መንጃ ፈቃድ በድጋሚ ካልመዘንኩህ አትሰራም ማለቱ ህጋዊ መሰረት የለውም በሚል የተተቸው ምዘናው ከ10 እስከ 30 ዓመታት ልምድ ያላቸውን ባለሙያዎች ስራ አስፈትቶ ማሰልጠንና አሽከርካሪዎች በሙሉ በገዛ ገንዘባቸው በድጋሚ እንዲሰለጥኑ መገደዳቸው አግባብነት እንደሌለው ቅሬታ ሲቀርብበት ቆይቷል።