የአሜሪካ ጦር ስልታዊ በሆነችው የኢራን የወደብ ከተማ ባንዳር አባስ አቅራቢያ በሚገኝ ወታደራዊ ይዞታ ላይ አዲስ እና ድንገተኛ የአየር ጥቃት መፈጸሙን ተከትሎ የኢራን አብዮታዊ ዘብ በኩዌት በሚገኝ የአሜሪካ የአየር ጦር ሰፈር ላይ የሚሳይል እና የሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) የአጸፋ እርምጃ መውሰዱን ይፋ አድርጓል።
ይህ ማለት ደግሞ አሁን ላይ ሁለቱ ሀገራት በቀጥታ ሚሳይል ወደ መተኮስ መሸጋገራቸውን ያሳየ ሲሆን ይህም ለአካባቢው ቀጠናዊ መረጋጋት እጅግ አደገኛ ምዕራፍ ከፋች ሆኗል።
አሜሪካ በኢራን ላይ ጥቃት ስትሰነዝር በሦስት ቀናት ውስጥ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን፤ ከሁለት ቀናት በፊትም በደቡባዊ ኢራን በሚገኙ የሚሳኤል ቤዞች እና ፈንጅ ሲቀብሩ ነበር ባለቻቸው ጀልባዎች ላይ ተመሳሳይ የአየር ድብደባ መፈጸሟ ይታወሳል።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በበኩሉ የተወሰደው እርምጃ በሆርሙዝ ሰርጥ ዓለም አቀፍ የባህር ትራፊክ ላይ ስጋት ፈጥረዋል የተባሉ አራት የኢራን ድሮኖችን ለማውደም የታለመ የቅድመ መከላከል ስትራቴጂ መሆኑን ገልጿል።
ይህ ወታደራዊ አሰላለፍ በመሬት ላይ ካለው ተጨባጭ የዲፕሎማሲ ጥረት እውነታ ጋር ፍጹም የሚጋጭ ሲሆን በተለይም ዋሽንግተን እና ቴህራን ጦርነቱን በዘላቂነት ለማቆም በሶስተኛ ወገን አማካኝነት ይጀምሩታል ተብሎ ይገመት የነበረውን የሰላም ድርድር ሙሉ በሙሉ አደጋ ላይ የጣለ ነው በመባል ወቀሳ እየቀረበበት ይገኛል።
አብዮታዊ ዘቡ በበኩሉ ለአሜሪካ ትንኮሳ የተሰጠው ምላሽ የመጀመሪያው ማስጠንቀቂያ ብቻ መሆኑን በመግለጽ "ዋሽንግተን ጠብ አጫሪነቷን የምትቀጥል ከሆነ የላቀ እና የበለጠ ወሳኝ እርምጃ ይጠብቃታል" ሲል ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ተቆጥቧል።

በሌላ በኩል በጥቃቱ ወቅት በኩዌት የአደጋ ጊዜ ድምጽ የተሰማ ሲሆን የኩዌት ጦር ግን የአየር መከላከያ ሥርዓቱ ወደ አየር ክልሉ የገቡ የጠላት ሚሳኤሎችን እና ሰው አልባ አውሮፕላኖችን በአየር ላይ እየጠለፈ ሲከላከል እንደነበር አስታውቆ ፍንዳታዎቹ በትክክል ከየት አቅጣጫ እንደመጡ ከመግለጽ ተቆጥቧል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የአሜሪካ እና የኢራን ፍጥጫ በዚህ መልኩ በሆነበት ሰዓት የእስራኤል እና የሊባኖስ ግንባርም ወደ ከፋ ሰብአዊ ጥፋት እያመራ ይገኛል።
ምንም እንኳን ይህ ተከታታይ ወታደራዊ እርምጃ ጠላት የተባሉትን ኃይሎች ለማዳከም እና የኃይል ሚዛኑን ለማስጠበቅ የሚደረግ ስሌት እንደሆነ በየጎራው ባሉ መንግሥታት በኩል ቢገለጽም አሁን ባለው ተጨባጭ የዓለም ጂኦፖለቲካ ሁኔታ ግን እንዲህ ዓይነት የኃይል እርምጃ በመካከለኛው ምስራቅ ላይ ከፍተኛ የስነ-ልቦና ጫና፣ የኤኮኖሚ ቀውስ እና ፍርሃትን ዳግም ፈጥሯል።