የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ልዑክ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ማሻሻያ ፕሮግራም ላይ 5ኛውን ግምገማ ለማካሄድ ለበርካታ ሳምንታት በአዲስ አበባ ቆይታ አድርጓል።
በዚህም ድርጅቱ የኢትዮጵያን ማክሮ ኢኮኖሚ ለማረጋጋት እና የፋይናንስ አቅምን ለማጠናከር በሚል፣ መንግስት ሊተገብራቸው የሚገቡ ሶስት ዋና ዋና ግዴታዎችን አስቀምጧል።
እነዚህም በውጭ ምንዛሬ ገበያ ውስጥ የብር የምንዛሬ ተመን በገበያ እንዲመራ የማድረግ ሂደቱ እንዲፋጠን፤ መንግስት ለተለያዩ አገልግሎቶችና ምርቶች የሚያደርገውን ቀጥተኛ ድጎማ በሂደት እንዲያስወግድ፣ እንዲሁም የሀገር ውስጥ የታክስ ገቢን በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ የሚያስችሉ ጠንከር ያሉ እርምጃዎችን እንዲወስድ የሚጠይቁ ናቸው።
የ IMF ዋና ዋና ግዴታዎች አፈጻጸም እንደሚከተለው በዝርዝር ሊታይ ይችላል፦
1. የብር የመግዛት አቅምን ማዳከም፡ የኢትዮጵያ ብር በውጭ ምንዛሬ ገበያ ላይ ያለው የዋጋ መዋዠቅ እንዲፋጠን ማድረግ ነው። ይህ እርምጃ የውጭ ምንዛሬ እጥረትን ለመቅረፍ እና ጥቁር ገበያን ለማስወገድ ያለመ ቢሆንም፣ የብርን የመግዛት አቅም በፍጥነት እንዲቀንስ በማድረግ የውጭ ግብዓቶች ዋጋ እንዲንር ያደርጋል።
2 የመንግስት ድጎማዎች መነሳት፡ መንግስት ለነዳጅ፣ ለኤሌክትሪክ እና ለሌሎች መሰረታዊ አገልግሎቶች የሚያደርገውን ቀጥተኛ ድጎማ በደረጃ እንዲያስቀር ነው። ይህም የመንግስትን በጀት ጫና ቢቀንስም፣ በሸቀጦችና አገልግሎቶች ላይ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ በመፍጠር የኑሮ ውድነቱን ያባብሰዋል።
የታክስ ገቢ ማሳደግ፡ መንግስት ከውጭ ብድር እና ዕርዳታ ማግኘት ጋር በተያያዘ የገጠመውን ፈተና ለመቋቋም፣ የሀገር ውስጥ ገቢን በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ የሚያስችሉ ጠንከር ያሉ እርምጃዎችን እንዲወስድ የሚጠይቅ ነው። ይህ ግዴታ የግብር መሠረቱን ማስፋትን እና የግብር አሰባሰብ ስርዓቱን ማጥበቅን ያካትታል።

በዚህም ታዲያ እነዚህ የፖሊሲ ማሻሻያዎች በኢትዮጵያ ህዝብ፣ በተለይም በተራው ዜጋ እና በንግዱ ማህበረሰብ ላይ ቀጥተኛ እና ፈታኝ ተጽዕኖዎችን ሊያሳድሩ ይችላሉ ተብሏል፡፡ የብር ዋጋ መዳከም የውጭ ምንዛሬን ተከትሎ የሚመጣውን የዋጋ ግሽበት በማፋጠን የኑሮ ውድነት እንዲባባስ ማድረጉ የዕለት ተዕለት እውነታ ሆኗል።
በሌላ በኩል፣ መንግስት የገቢ ምንጮቹን ለማስፋት እና የግብር አሰባሰብ ስርዓቱን ለማጥበቅ የሚወስዳቸው እርምጃዎች፣ በኢኮኖሚው ጫና ውስጥ ላለ ህዝብ ተጨማሪ ሸክም መሆኑ አይቀሬ እንደሆነ ግልጽ ነው።
የታክስ አስተዳደሩ ደንቦች እየጠነከሩ በመምጣታቸው፣ የህግ ማስከበር ስራው ከጤናማ የግብር ስርዓት ይልቅ የገቢ ማሳደጃ ወይም "ገቢ አደን" መልክ ይይዛል የሚል ስጋትም በሰፊው እየተነሳ ነው።
በአጠቃላይ፣ እነዚህ እርምጃዎች ለመንግስት የፊስካል አቅም ማጠናከሪያ እንደ መልካም ዕድል ቢታዩም፣ የህዝቡን የመክፈል አቅም እና የኑሮ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ ካልተመሩ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ቀውሶችን ሊጋብዙ እንደሚችሉ ይታመናል።