በዩክሬን መንግስት የስለላ ተቋም ስር የሚንቀሳቀሰው “I Want to Live” የተሰኘው ፕሮጀክት በሩሲያ እና በዩክሬን ጦርነት ውስጥ እየተሳተፉ ነው ያላቸውን የ34 ኢትዮጵያውያን ስም ዝርዝር ይፋ አድርጓል።
ለሩሲያ ጦር ተሰልፈው የሚዋጉ ኢትዮጵያውያንን ስም ይፋ ያደረገው ፕሮጀክቱ ከእነዚህ መካከል ቢያንስ 3ቱ መሞታቸውን አስታውቋል።
ፕሮጀክቱ እነዚህ ኢትዮጵያውያን ለሩሲያ ጦር ኃይል የፈረሙት በተለያየ ጊዜ ሲሆን እ.ኤ.አ ዲሴምበር 24 ቀን 2024 ዓ.ም 8ቱ፣ ሴፕቴምበር 1 ቀን 2025 ደግሞ 10ሩ፣ እንዲሁም ኦክቶበር 30 ቀን 2025 በተመሳሳይ 9 ሰዎች ኮንትራት መፈጸማቸውን አስፍሯል።
እነዚህ ኢትዮጵያውያን ኮንትራቱን የፈረሙት በቀጥታ ከሩሲያ ጦር ኃይል ጋር ሳይሆን፤ በሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች አማካኝነት እንደሆነ ተገልጿል።
ይፋ ከሆኑት 34ቱ ግለሰቦች መካከል በእድሜ ትንሹ የሆኑት አዱኛ አሮንና ዘለቀ ናትናኤል መሆናቸውን ገልጾ፤ እድሜያቸው በ20ዎቹ መጀመሪያ ላይ እንደሚገኝ ጠቅሷል።
በእድሜ ትልቁ ደግሞ ሀብተማሪያም ስንታየሁ የተባሉ ግለሰብ መሆናቸውንና እድሜያቸውም 50 ዓመት መሆኑን በማስቀመጥ አነጻጽሯል።
ፕሮጀክቱ እንዳለው የእነዚህን 34 ኢትዮጵያውያን ስም ለማወቅ የቻለ ቢሆንም በሩሲያ ጦር ኃይል ውስጥ ተሰልፈው እየተዋጉ ያሉ ኢትዮጵያውያን ግን በርካታ ናቸው ተብሏል።
አክሎም እስካሁን ባለው መረጃ ከ40 የአፍሪካ አገራት የተውጣጡ 2,984 ሰዎች ለሩሲያ እየተዋጉ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ 6ቱ ሕይወታቸው ማለፉን ለመረዳት መቻሉን አስታውቋል።
በሌላ በኩል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭን በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው በትናንትናው እለት አነጋግረዋል፡፡
ከሁለት አመት በፊት በሩሲያ እና በዩክሬይን መካከል በተቀሰቀሰው ጦርነት ሳቢያ ዓለም አቀፍ ትኩረት በአዲስ አበባ በሚገኘው የሩሲያ ኤምባሲ ላይ አርፎ እንደነበር ይታወሳል።
በዚህም በመቶዎች የሚቆጠሩ የቀድሞ የኢትዮጵያ ወታደሮች በሩሲያ ጦር ሰራዊት ውስጥ ተሰልፈው ለመዋጋት ያላቸውን ፍላጎት ለመግለጽና ዝርዝር መረጃቸውን ለማስገባት በኤምባሲው ደጃፍ ረጅም ሰልፍ ፈጥረው ነበር።
በስፍራው የተገኙት አመልካቾች በወቅቱ በሩሲያ በኩል ምዝገባ እየተካሄደ እንደሆነ እንደሰሙ ገልጸው የነበረ ሲሆን የሩሲያ ኤምባሲ በበኩሉ እነዚህ ሰዎች የተሰለፉት ለውትድርና ምልመላ ሳይሆን ለሩሲያ ፌዴሬሽን ያላቸውን አጋርነት ለመግለጽ መሆኑን አስታውቆ ነበር።
የኢትዮጵያ መንግሥት በወቅቱ በጉዳዩ ላይ ይፋዊ መግለጫ ያልሰጠ ሲሆን፤ ኤምባሲው መግለጫውን ከሰጠ በኋላ በስፍራው የነበረው ውጥረት ቀዝቀዝ ብሎ ነበር።
ይሁን እንጂ ክስተት በወቅቱ በኢትዮጵያዊያን የቀድሞ ወታደሮች ዘንድ የነበረውን ከፍተኛ የኢኮኖሚ ተፅዕኖና የስራ አጥነት ችግር በማሳየቱ በብዙዎች ዘንድ አነጋጋሪ ሆኖ ነበር።