በደቡብ አፍሪካ በስደተኞች ላይ እየደረሰ ያለው የፀረ-ስደተኛ ጥቃት እና የተለያዩ አክቲቪስት ቡድኖች እስከ June 30, 2026 የጣሉት የ"ቀነ-ገደብ" ማስፈራሪያ ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ አፍሪካውያን ስደተኞች ሀገሪቱን በከፍተኛ ፍርሃት እየለቀቁ ይገኛሉ።
የጥላቻ ንግግሮች ወደ አካላዊ ጥቃትና ግድያ መቀየራቸው ለዚህ መጠነ-ሰፊ መፈናቀል ዋነኛ ምክንያት የሆነ ሲሆን ይህንን አስቸጋሪ ሁኔታ ተከትሎ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች በስደተኞች ተጨናንቀዋል።
እንደ ዓለም አቀፍ የዜና ምንጮች ዘገባ በባህር ዳርቻ አካባቢዎች በተፈጸሙ ጥቃቶች የሁለት ሞዛምቢክ ዜጎች ህይወት ያለፈ ሲሆን አንድ የማላዊ ዜጋም በድንጋይ ተወግሮ መገደሉ ተረጋግጧል። ከዚህም በላይ ከ50 በላይ የመኖሪያ ቤቶች በእሳት መቃጠላቸው ተመዝግቧል።
በተለይም በደርባን ከተማ በሚገኘው መጠለያ ጣቢያ ብቻ እስከ 10,000 የሚደርሱ ስደተኞች የተጠለሉ ሲሆን በቦታው ያለው የንጽህና መጠበቂያ፣ የምግብ እና የውሃ አቅርቦት እጥረት ከፍተኛ የጤና ስጋት ፈጥሯል።
የናይጄሪያ፣ የጋና፣ የሞዛምቢክ እና የማላዊ መንግስታት ዜጎቻቸውን በልዩ በረራዎች እና በየብስ ኮንቮዮች ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጥረት እያደረጉ ሲሆን እስካሁን ወደ 2,000 የሚጠጉ ዜጎች በአየር መንገድ፤ ሌሎች በሺዎች የሚቆጠሩት ደግሞ በየብስ ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል።
የደቡብ አፍሪካ መንግስት በበኩሉ June 30 መደበኛ የሥራ ቀን እንደሚሆን በይፋ ያስታወቀ ሲሆን የፍትህ ሚኒስትሯ ማማሎኮ ኩባዪ ማንም ግለሰብ ወይም ቡድን ህጋዊ መብት ሳይኖረው የሌላ ሰውን ማንነት የመጠየቅ ወይም የመፈተሽ ስልጣን የለውም ብለዋል።በዚህም መንግስት ማንኛውንም አይነት ማስፈራሪያ ወይም ሁከት ላይ ጠንካራ የህግ እርምጃ እንደሚወስድ አስጠንቅቋል።
ፕሬዝዳንት ሲሪል ራማፎሳ በበኩላቸው ስደተኞችን ለፖለቲካዊ ዓላማ እና ለኢኮኖሚ ቀውስ መሸፈኛነት መጠቀም ተገቢ አለመሆኑን ገልጸው የደህንነት አካላት ሰኔ 30ን ተከትሎ ሊከሰት የሚችል ማንኛውንም ሁከት ለመቆጣጠር በከፍተኛ ዝግጅት ላይ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በደቡብ አፍሪካ እየተከሰተ ባለው የጥላቻ ጥቃት ስጋታቸውን በመግለጽ ተጋላጭ የሆኑ ማህበረሰቦችን ለመጠበቅ እና የጥላቻ ንግግሮችን ለማስቆም ጥሪ አቅርበዋል።
በሌላ በኩል በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ ጥቃቶች ሊፈፀሙ የሚችሉበት አዝማሚያ ስላለ ኢትዮጵያውያን ጥንቃቄ የተሞላበት እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ በደቡብ አፍሪካ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ ከሰሞኑ ማሳሰቡ ይታወሳል።
በደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵያ ኢምባሲ በሀገሪቱ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ እየተከታተለና ከመንግስት ጋር አስፈላጊውን ግንኙነት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ያስታወቀ ሲሆን የደቡብ አፍሪካ መንግስት በስደተኞች ላይ የኃይል ጥቃቶች እንዳይደርሱ በሁሉም አካባቢዎች ተገቢውን ጥበቃ እንዲያደርግ አስታውሷል።
ስለዚህም በመላው ደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በስደተኞች ላይ ሊደርሱ የሚችሉ የመብት መጣስ መሰረት በማድረግ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸውን እንዲያደርጉ ያሳሰበ ሲሆን ከሚኖሩበት አካባቢ የመንግስት አካላት እና የኮሚኒቲ አደረጃጀቶች ጋር የቅርብ ግንኙነት እንዲያደርጉ፣መረጃዎችንም እንዲለዋወጡ እንዲሁም አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።
ደቡብ አፍሪካ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ በተደጋጋሚ መሰል የጥላቻ ጥቃቶች የሚከሰቱባት ሀገር ስትሆን የአሁኑ ቀውስ በዋናነት የተያያዘው በስራ አጥነት በኢኮኖሚ አለመረጋጋት እና በሀብት ክፍፍል ኢ-ፍትሃዊነት ነው።