አስከፊ የኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ በምትገኘው የመን ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች በዝቅተኛ የጉልበት ሥራ ዘርፎች ከእነሱ ያነሰ ክፍያ በሚቀበሉ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች እየተተኩ መሆኑን በመግለጽ ቅሬታ አሰምተዋል።
በየመን የወጣቶች ሥራ አጥነት መጠን 32.39 በመቶ የደረሰ ሲሆን ይህ ቀውስ በተለይ ልዩ ክህሎትና የከፍተኛ ትምህርት ደረጃ በሌላቸው ወጣቶች ላይ ይታያል።
ከአምስት ዓመታት በፊት ከተቀሰቀሰው የእርስ በርስ ጦርነትና የኢኮኖሚ ውድቀት በኋላ የመናውያን ወጣቶች ቤተሰቦቻቸውን ለማስተዳደር በማንኛውም ዝቅተኛ የጉልበት ሥራ ላይ ለመሰማራት ቢገደዱም አሁን ላይ ግን ያንን ማግኘት አስቸጋሪ እየሆነባቸው መጥቷል።
በዚህም ላለፉት 15 ዓመታት በአደን ከተማ በሚገኙ ምግብ ቤቶች ውስጥ ሰሃን በማጠብና በጽዳት ሥራ ይተዳደር የነበረ የመናዊ አሁን ግን ሥራ አጥ መሆኑን እንደገለጸ ሚድል ኢስት አይ አስነብቧል።
ግለሰቡ በወር ያገኝ የነበረው 130,000 የየመን ሪያል የነበረ ሲሆን በ80,000 የየመን ሪያል ለመሥራት በተስማማ ኢትዮጵያዊ ስደተኛ ተተክቻለሁ ብሏል።
አያይዞም የኢትዮጵያ ስደተኞች እዚህ ሀገር ቤተሰብ ስለሌላቸው ለሕይወት ማቆያ የሚሆን ማንኛውንም አነስተኛ ክፍያ ይቀበላሉ ያለው ግለሰቡ እኛ ግን ቤተሰብ ስላለን ያ ክፍያ አይበቃንም ሲል አብራርቷል።
በተጨማሪም ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ጠንክረው ስለሚሠሩ፣ የተሻለ ስለሚያጸዱና ያነሰ ክፍያ በመቀበል ረጅም ሰዓት ያለ ምንም ቅሬታ ስለሚሰሩ በነጋዴዎች ተመራጭ መሆናቸው ተገልጿል።
ኢትዮጵያዊያን በበኩላቸው ዋናው እቅዳቸው ሳዑዲ ዓረቢያ መድረስ መሆኑን በመግለጽ በሃገሪቱ በሚቆዩበት ሰአት ለምግብ እንዲሁም ለተለያዩ ነገሮች የሚያስፈልጋቸውን ወጭዎች ለመሸፈን እንደሚሰሩ ያስረዳሉ።
በተጨማሪም በቦታው የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን የመናውያን ወንድሞቻችን ናቸው፤ አንድ ዓይነት ስቃይ ነው የምንጋራው ማለታቸውን ዘገባው ጠቅሷል።
የዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (IOM) መረጃ እንደሚያሳየው እ.ኤ.አ በ2025 ብቻ 110,144 ስደተኞች ወደ የመን የገቡ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 97 በመቶዎቹ የኢትዮጵያ ዜጎች ናቸው።
የመን ወደ ሳዑዲ ዓረቢያና ሌሎች የባሕረ ሰላጤው አገራት ለሚደረግ አደገኛ ጉዞ ዋነኛ የመሸጋገሪያ አገር ሆና የምታገለግል ሲሆን ወደ አገሪቱ ከሚገቡት ስደተኞች መካከል 90 በመቶ ያህሉ ግባቸው ሳዑዲ ዓረቢያ መድረስ ሲሆን ቀሪዎቹ 10 በመቶዎቹ ግን የመን ውስጥ ይቆያሉ።
ይሁን እንጂ የስደተኞቹ መፍለስ የመን ውስጥ ላለው አጠቃላይ ሥራ አጥነት ዋና መንስኤ ባይሆንም በተወሰኑ ዘርፎች በተለይም በጽዳት በቤት ውስጥ የጉልበት ሥራዎችና በእርሻዎች ላይ ፍጹም ያልተመጣጠነ የገበያ ውድድር ፈጥሯል።
ቀደም ሲል የመናውያን ባህላዊ እሴትን መሠረት በማድረግ የጽዳት ሥራዎችን የመናቅ አዝማሚያ የነበረባቸው ሲሆን አሁን ያለው አስከፊ የኢኮኖሚ ቀውስ ግን ያንን ባህል አጥፍቶት ወጣቶቹ ማንኛውንም የሥራ ዕድል እንዲፈልጉ ማስገደዱ ለዚህ ቅሬታ አብቅቷቸዋል።
በሌላ በኩል በርካታ የቱኒዚያ ዜጎች ቅዳሜ ዕለት በመዲናዋ ቱኒስ በሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የከፍተኛ ስደተኞች ኮሚሽን ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት በመሰብሰብ ሰነድ የሌላቸው ከሰሃራ በታች ያሉ አፍሪካውያን ስደተኞች በአስቸኳይ ከሀገር እንዲባረሩ እና ድርጅቱም ቱኒዚያን ለቆ እንዲወጣ የሚጠይቅ የተቃውሞ ሰልፍ አድርገዋል።