የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን (EFDA) በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ መድረኮች እና ዋና ዋና የመገናኛ ብዙኃን ላይ ያለቅድመ ምርመራና ይፋዊ ፍቃድ እየተሰራጩ የሚገኙ የህክምና መገልገያ መሳሪያዎች ማስታወቂያዎችን በአስቸኳይ እንዲያቆሙ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።
ባለስልጣኑ ይሄንን ማስጠንቀቂያ የሰጠው ዛሬ ሰኔ 24/2018 ዓ.ም በማህበራዊ ትስስር ገጹ ያለአግባብ የሚከናወኑ የህክምና መገልገያ መሳሪያዎች ማስታወቂያና ቅስቀሳ በተመለከተ ባስተላለፈው መልዕክት ነው።
አንዳንድ ማስታወቂያዎች በህግ ከተቀመጠው አግባብ ውጪ የሚከናወኑ ከመሆናቸውም በላይ፤ በአሁኑ ወቅት በማህበራዊ ሚዲያ መድረኮች ላይ የሚተላለፉ ማስታወቂያዎች የተከለከሉ የህክምና መሳሪያዎችን ጭምር የሚያስተዋውቁ መሆናቸውን ባለልስጣኑ ታዝቧል።
ይህ ህገ-ወጥ ድርጊት የህዝብን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ፤ ሁሉም የሚመለከታቸው አካላት ተገቢው ህጋዊ እርምጃ ከመወሰዱ በፊት ማስታወቂያዎቹን እንዲያስወግዱ ባለስልጣኑ አሳስቧል።
ባለስልጣኑ ይህንን እርምጃ የወሰደው በምግብና መድኃኒት አስተዳደር አዋጅ ቁጥር 1112/2019 አንቀጽ 4 በተሰጠው ሥልጣን መሰረት የህክምና መገልገያ መሳሪያዎችን ደህንነት፣ ጥራትና አቅም የመቆጣጠር ሃላፊነቱን ለመወጣት መሆኑን አብራርቷል።
በዚህም በአዋጁ አንቀጽ 58 እና 59 ማንኛውም የህክምና መሳሪያ ማስታወቂያና ቅስቀሳ በባለስልጣኑ ጥብቅ ቁጥጥርና ግምገማ ስር ማለፍ እንዳለበት ሰፍሯል።
በተለይም ህጉ በጤና ተቋማት ውስጥ ያለፈቃድ ማስተዋወቅን እንዲሁም ለጤና ባለሙያዎች የሚደረጉ ህገ-ወጥ የጥቅማጥቅም ስጦታዎችን በጥብቅ የሚከለክል ሲሆን የህክምና መሳሪያ ማስታወቂያዎችን የሚያከናውኑ አካላትም በባለስልጣኑ በኩል ህጋዊ ፈቃድ ያላቸው መሆን እንዳለባቸው በአዋጁ ተደንግጓል።
ከዚህ ቀደም የባለስልጣኑ የህክምና መሳሪያ ግምገማና ገበያ ፈቃድ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስሪያ ቤት ለተመረጡ የህክምና መገልገያ መሳሪያዎች የማስታወቂያ ፍቃድ ሲሰጥ መቆየቱን አስታውቋል።
ይህ የሚከናወነው ለቀረቡ የማስታወቂያ ይዘቶች አስፈላጊው የጥራትና የደህንነት ግምገማ ከተደረገ በኋላ ነው ያለው ባለስልጣኑ ነገር ግን አሁን እየታየ ያለው ሁኔታ ይህንን ህጋዊ አሰራር የጣሰ በመሆኑ ከዚህ በኋላ የሚከናወኑ ማስታወቂያዎች በሙሉ ባለስልጣኑ በሚሰጠው ይፋዊ የፍቃድ ደብዳቤ ብቻ እንዲገደቡ አዝዟል።
በመጨረሻም ባለስልጣኑ የቲክቶክ፣ የዩቲዩብ፣ የፌስቡክ እና ሌሎች ማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች እንዲሁም የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት ከዚህ ማሳሰቢያ በኋላ ማስታወቂያዎችን በማስተላለፍ ሂደት ላይ ጥብቅ ቁጥጥር እንዲያደርጉ አሳስቧል።
የትኞቹም አካላት ይህንን የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ በመጣስ ያለባለስልጣኑ ፍቃድ ማስታወቂያቸውን የሚቀጥሉ ከሆነ፤ በህጉ መሰረት ተገቢውን እርምጃ እንደሚወስድ ባለስልጣኑ አስታውቋል።
በተጨማሪም ባለስልጣኑ ለወደፊቱም የህክምና መሳሪያዎች በህጋዊ መንገድ እና በጥራት መመዘኛዎች መሰረት ብቻ መተዋወቃቸውን ለማረጋገጥ የማያቋርጥ ቁጥጥር እንደሚያደርግ ጠቁሟል።